የልጅነት ጊዜያቸውን በጭንቀት የሚያሳልፉ ልጆች በወደፊት እድሜያቸው ለ??

የልጅነት ጊዜያቸውን በጭንቀት የሚያሳልፉ ልጆች በወደፊት እድሜያቸው ለደም ግፊት ተጋላጭ ይሆናሉ ተባለ

 

 

የልጅነት እድሜያቸውን በከፍተኛ ጭንቀት ውስጥ የሚያሳልፉ ልጆች እድሜያቸው እየጨመረ ሲሄድ ለከፍተኛ የደም ግፊት ተጋላጭ እንደሚሆኑ አዲስ የወጣ ጥናት አመልክቷል።

ሌላ የወጣ አዲስ ጥናት ደግሞ ወላጆቻቸው በወጣትነት እድሜ ለደም ግፊት የተጋለጡ ከሆነ ከእነሱ የሚወለዱ ልጆችም ለደም ግፊት ተጋላጭነታቸው የጨመረ መሆኑን ያሳያል።

በመጀመሪያው የጥናት ውጤት ላይ ስናተኩር ለከፍተኛ ጭንቀት የተጋለጠ ህጻናት በወደፊት እድሜያቸው ለከፍተኛ የደም ግፊት እና ለልብ ህመም ተጋላጭነት ይስተዋልባቸዋል ተብሏል።

በጆርጂያ አውጉስታ ኮሌጅ ኦፍ ሜዲስን ተባባሪ ፕሮፌሰር የሆኑት ሻዎዮንግ ሱ፥ “የልጅንት እድሜያቸውን በጭንቀት ውስጥ ያላሳለፉ ሰዎች የዲያስቶሊክ የደም ልኬት

በአማካኝ 60 ነው ያሉ ሲሆን፥ በጭንቀት ውስጥ ያሳለፉ ከሆነ ግን የዲያስቶሊክ የደም ልኬት መጠኑ እስከ 65 ይደርሳል” ብለዋል።

ይህም በጣም ትልቅ ልዩነት አለው ሲሉም ተባባሪ ፕሮፌሰር ሻዎዮንግ ሱ ይናገራሉ።

“ዲያስቶሊክ” የደም ግፊት ልኬት ማለት የታችኛው የደም ልኬት ቁጥር ሲሆን፥ “ሳይሰቶሊክ” የሚባለው ደግሞ የላይኛው የደም ግፊት ልኬት ቁጥር በመባል ነው የሚታወቀው።

ለምሳሌም የአንድ ጤናማ ሰው የደም ግፊት መጠን 120/80 ከሆነ፤ 120 የላይኛው ልኬት ወይም “ሳይስቶሊክ” ሲባል፤ 80 ደግሞ የታችኛው ወይም “ዲያስቶሊክ” በመባል ይጠራል።

ወደ ሁለተኛው የጥናው ውጤት ስንመለስ፥ የቤተሰቦቻቸው እድሜ ከ55 ዓመት በፊት እያለ ለደም ግፊት የተጋለጡ ከሆነ ልጆቻቸው እንደ ቤተሰቦቻቸው ለደም ግፊት የመጋለጥ እድል አላቸው የተባለ ሲሆን፥ በዚህ ዙሪያ ግን ጠለቅ ብሎ የተያዘ ነገር የለም።

ተመራማሪዎች ለመጀመሪያው የጥናት ውጤት ማለትም በጭንቀት ውስጥ የሚያድጉ ልጆች ላይ የሚከሰት የደም ግፊትን ለመለየት በ373 ተሳታፊዎች ላይ ምርመራ ያደረጉ ሲሆን እነዚህም እድሜያቸው ከ7 እስከ 38 መካከል የሆኑ ናቸው።

በዚህም የተሳታፊዎቹን የእምሮ ሁኔታ በቀን ይሁን በእንቅልፍ ሰዓት በህልም እየታያቸው የሚያስጨነቃቸው ነገሮች ላይ ክትትል አድርገዋል።

ክትትሉንም ለ23 ዓመታት በተከታታይ ማድረጋቸውን የሚናገሩት ተመራማሪዎቹ፥ በተጨማሪም ተሳታፊዎቹ በልጅነት ጊዜያቸው ለደም ግፊት ለጭንቀት ይዳርጋሉ በተባሉ የጉልበት ብዝበዛ እና አስፈሪ ነገሮች ውስጥ ማሳለፋቸውን፣ ሁሌም በሚጣሉ ቤተሰቦች እና ዝቅተኛ የኢኮኖሚ ኑሮ ባለበት አካባቢ መኖር አለመኖራቸውንም ለይተዋል። 

በዚህም በልጅነት ጊዜያቸው ለሚያስጨንቁ ነገሮች ተጋልጠው ያደጉ ልጆች በቀላሉ ለከፍተኛ የደም ግፊት የተጋለጡ ናቸው ተብሏል።

በጥናቱ ውጤት መሰረትም በጭንቀት ውስጥ ያደጉ ልጆን ለደም ግፊት የመጋለጥ እድላቸው ከሌሎች ጋር ሲነጻጸር የመጋለጥ እድላቸው በ17 በመቶ የጨመረ ነው ሲሉም ተባባሪ ፕሮፌሰር ሱ አስታውቀዋል።

 

ምንጭ፦ www.upi.com/Health